የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትር ክቡር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በደቡብ ኦሞ ዞን የቀይ አፈር 2ኛ ደረጃ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከል ግንባታን በይፋ አስጀመሩ።
የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትር ክቡር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፣ በደቡብ ኦሞ ዞን ናፀማይ ወረዳ ቀይ አፈር ከተማ ለሚገነባው ‘የቀይ አፈር 2ኛ ደረጃ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከል’ የመሠረት ድንጋይ በማኖር የግንባታ ሥራውን በይፋ አስጀምረዋል።
ይህ ግንባታ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የገበያ መሠረተ ልማት ስብራትን ለመጠገንና የንግድ ሥነ-ምህዳሩን እስከ ታችኛው መዋቅር ድረስ ለማዘመን የጀመረው ስትራቴጂካዊ ጉዞ አካል ነው። በዓለም ባንክ የፋይናንስ ድጋፍ በDRIVE ፕሮጀክት የሚገነባው ይህ ማዕከል፣ የቁም እንስሳት ንግድ ሥርዓቱን በማዘመን አርብቶ አደሩ ከምርቱ ተገቢውን ዋጋ እንዲያገኝ የሀገሪቱ የውጭ ንግድ ገቢ እንዲያድግ ከፍተኛ አቅም የሚፈጥር ነው።
ሚኒስቴሩ በተመሳሳይ በሞያሌ ቢቃ መሰል ግንባታዎችን የጀመረ ሲሆን፤ በደገሀቡር፣ በሰመራ እና በኤልብኮ የሚገኙ ፕሮጀክቶችም በመጠናቀቅ ላይ ይገኛሉ።
በቅርቡም የዚሁ ፕሮጀክት አካል የሆነውን በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ የጄሙ ግብይት ማዕከል ግንባታ ሥራ የሚጀመር ይሆናል።










